ታሪኩ የተፈጸመው በሕንድ ከአንድ መቶ ሐምሳ አመት በፊት ነው። በዌልስ ፤ እንግሊዝ በነበረው ከፍተኛ ወንጌል መነቃቃት ወንጌልን ወደ ተቀረው አለም ለማድረስ የወንጌል መልዕክተኞች ከዌልስ ወደ ሰሜን ምስራቅ ሕንድ አሳም ወደሚባል ስፍራ ያመራሉ። አሳም ከመቶ በላይ ከመቶ በላይ ነገዶች የሚኖሩባት እና ባህላዊ እና ኋላ ቀር ኑሮን የሚኖሩ ሰዎች የነበሩባት ስፍራ ነበረች። ታዲያ እነዚህ የዌልስ ወንጌል ሰባኪያን ለዚህ ሕዝብ ፍቅርን ፣ ሰላምን እና በክርስቶስ ኢየሱስ የሚገኘውን ተስፋ መናገር ጀመሩ። ህዝቡ አልተቀበላቸውም ነበር።
ከቆይታ በኋላ አንድ የዚያ አከባቢ ተወላጆች የሆኑ አንድ ቤተሰብ በዌልሶቹ የወንጌል ምስክርነት ክርስትናን ተቀበሉ። ከቤተሰቡ ቀድሞ ክርስትናን የተቀበለው አባት ነበር። ከዚያም ሚስት እና ሁለት ልጆች ቀጥለው ተቀበሉ። እንዲህ እያለ የዚህ አባት ምስክርነት ብዙ የአሳም ነዋሪዎች ክርስትናን እንዲቀበሉ ምክንያት ሆነ። ይህ በመሆኑ ደስተኛ ላልነበረው የአከባቢው የነገዶቹ አለቃ የዚህን ቤተሰብ አባላት በሙሉ አስጠርቶ ክርስትናን ካዱ አለበለዚያ ግን ትገደላላችሁ ብሎ ያስፈራራቸዋል።
የዚህን ጊዜ አባት በመንፈስ ቅዱስ ተሞልቶ "የጌታን መንገድ እከተላለሁ። ወደ ኋላ አልመለሰም" ብሎ ዘመረ። የሰውየውን አሻፈረኝ ማለት የተመለከተው አለቃም ሁለቱን የሰውየውን ልጆች በቀስት እንዲገደሉ ትዕዛዝ ሰጠ። ልጆቹም ተገደሉ። አሁንም አለቃው ወደ አባትየው ዞሮ "አሁንስ እምነትህን አትክድም? ልጆችህን አጥተሃል። አሁን ደግሞ ሚስትህን ታጣለህ!" ብሎ ዛተበት።
አባትየው ግን አሁንም በመንፈስ ቅዱስ ተሞልቶ "ሁሉ ቢተውህ እኔ አልተውህም። ወደ ኋላ አልመለስም" ብሎ ዘመረ። ይህንን ያየው አለቃም የሰውውየው ሚስት አስገደለበት። በመጨረሻም "አንድ እድል ብቻ ሰጥሃለሁ እምነትህን ክደህ በሕይወት እንድትኖር" አለው።
አባ ግን አሁንም "መስቀል ከፊቴ አለም ከኋላ። ወደኋላ አልመለስም!" አለ። ሰውየው ልክ እንደ ሚስቱ እና ሁለት ልጆቹ ሁሉ በቀስት ተመቶ ተገደለ። አስገራሚው ጉዳይ ግን በሰውየው ጽናት የተገረመው የነገዶቹ አለቃ ራሱ ክርስቶስን አምኖ ይቀበላል። ያ አባት የዘመረው መዝሙር ዛሬ በአለም ላይ ተወዳጅ ከመሆኑም በላይ አማርኛን ጨምሮ በብዙ ሃገር ቋንቋዎች ተተርጉሞ ይዘመራል። ጽናት!
ሐዋርያው ጳውሎስም በመጨረሻዎቹ ቀናት ሞት የሚባል ትልቅ ተግዳሮት ከፊት ወጥቶ ነበር። ሞት ጽናትን የሚፈታተነው ትልቁ ተግዳሮት ነው። ሐዋርያው ጳውሎስ ይህንን ተግዳሮት ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ስም በጽናት ለማፍ የቆረጠ ነበር (2ኛ ጢሞቴዎስ 4:6)። ክርስቶስን በሞቱ እንኳ እንዲመስለው ይናፍቅ ነበርና (ፊልጵስዩስ 3:10) ።
ስለ ክርስቶስ መሞት ብርቅ የሆነብን ስለ ክርስቶስ መኖር ስላልደፈርን ነው። እንደ ሐዋርያው ስለ ክርስቶስ ስንኖር ወይም ክርስቶስ በእኛው ውስጥ እንዲኖር ስንፈቅድለት ስለ ክርስቶስ መሞትን እንማራለን። ያን ጊዜ ጽናትን ከሕይወት ብቻ ሳይሆን ከሞትም እንማራለን!
ስለ ክርስቶስ መሞት ብርቅ የሆነብን ስለ ክርስቶስ መኖር ስላልደፈርን ነው።
ጳውሎስን ከጎኑ ቆሞ ያበረታ እና ያጸና አምላክ (የሐዋርያት ሥራ 23፡11) እኛንም ያበርታን ደግሞም ያጽናን! አሜን!
IntroductionDay 1 Day 2Day 3Day 4Day 5Day 6Day 7Day 8