ማስወገድ:- ልክ ያልሆነ መሻትን ሊቀሰቅሱባችሁ የሚችሉ እይታዎችን እና ሁኔታዎችን ሊሆን በሚችል እና በተቻላችሁ መጠን አስወግዱ። “ሊሆን በሚችል እና በተቻላችሁ መጠን” ያልኩበት ምክንያት አንዳንድ ለፈተና የሚያጋልጡ ነገሮችን ማስወገድ ስለማይቻል ነው። “ልክ ያልሆነ መሻት” ያልኩበት ምክንያት ደግሞ ስለ ወሲብ ፣ ምግብ እና ቤተሰብ ያሉን መሻቶች ሁሉ መጥፎ ስላልሆኑ ነው። የማይጠቅሙን እና ልክ ያልሆኑ ባሪያ ሊያደርጉን ሲጀምራቸው እናውቃቸዋለን። ድካማችንን እና ምን እንደሚያስነሳቸውም ደግሞ እናውቃለን። “ማስወገድ” መጽሐፍ ቅዱሳዊ ስልት ነው። “ከክፉ የጎልማሳነት ምኞት ግን ሽሽ በንጹሕም ልብ ጌታን ከሚጠሩ ጋር ጽድቅን እምነትን ፍቅርን ሰላምን አጥብቀህ ተከተል” (2 ጢሞቴዎስ 2፡22)። “ምኞቱንም እንዲፈጽም ለሥጋ አታስቡ” (ሮሜ 13፡14)።
እንቢ በሉ:- ለሚመጡባችሁ የምኞት ሃሳቦች ሁሉ በ 5 ሰከንዶች ውስጥ እንቢ በሉ። ይህንንም በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ሥልጣን አድርጉት። በኢየሱስ ስም እንቢ! በሉት። ከአምስት ሰከንድ የሚበልጥ ጊዜ የላችሁም። እሰቲ ሳትቃወሙት ከዚያ በላይ ጊዜ ስጡት። ልታነቃንቁት እስካትችሉ ድረስ በታላቅ ኃይል መጥቶ መኖር ይጀምራል። ካስፈለጋችሁ ድምጽ አውጥታችሁ በሉት። ጠንካራ እና እንደ ጦረኛ ሁኑ። ጆን ኦውን እንዳለው “ኃጢያትን ግደሉት አሊያም ኃጢያት እራሱ ይገድላችኋል”። በኃይል አጥቁ። “ዲያብሎስን ግን ተቃወሙ ከእናንተም ይሸሻል” (ያዕቆብ 4፡7)።
ኃጢያትን ግደሉት አሊያም ኃጢያት እራሱ ይገድላችኋል
ጆን ኦውን
መልሱ:- ክርስቶስን የእርካታችሁ ጥግ በማድረግ ልባችሁን ወደ እርሱ መልሱ። እንቢ ማለት ብቻ በቂ አይሆንም። ከመከላከል ወደ ማጥቃት መሸጋገር አለባችሁ። እሾህን በእሾህ እንደሚባለው የኃጢያትን ተስፋዎች በክርስቶስ ተስፋዎች ተዋጓቸው። ኃጢያት ስለሚዋሸን መጽሐፍ ቅዱስ በ ኤፌሶን 4፡22 ላይ “የሚያታልል ምኞት” ይለዋል። ሊሰጡን ከሚችሉት በላይ ቃል ይገቡልናል። መጽሐፍ ቅዱስ “ባለማወቃችሁ አስቀድሞ የኖራችሁበትን ምኞት” (1 ጴጥሮስ 1፡14) ይላቸዋል። ሞኞች ብቻ ናቸው እጅ የሚሰጡት። “እርሱ እንዲህ ስቶ ይከተላታል፥ በሬ ለመታረድ እንዲነዳ” (ምሳሌ 7፡22)። ማታለል የሚሸነፈው በእውነት ብቻ ነው። አለማወቅ የሚሸነፈው በአውቀት ነው። ይህ እውነት ታላቅ እና የሚያምር እውነት መሆን አለበት። ለዚህም ነው “Seeing and Savoring Jesus Christ” የሚለውን መጽሐፌን የጻፍሁት። ልባችንን ታላላቅ በሆኑ በኢየሱስ ተስፋዎች እና ደስታዎች ማስታጠቅ አለብን። “እንቢ!” እንዳልን ወዲያው ወደ እነዚህ መዞር አለብን።
መያዝ:- ሌሎችን ምስሎች እስኪያስወጣ ድረስ የክርስቶስን ተስፋዎች እና ደስታዎች አጥብቃችሁ በልባችሁ ያዙ። “ኢየሱስን ተመልከቱ” (ዕብራውያን 12፡2)። ብዙዎች የሚወድቁት አዚህ ጋር ነው። ወዲያው እጅ ይሰጣሉ። “ለማስወጣት ሞከርኩ ግን አልሆነልኝም” ይላሉ። ከዚያም እጠይቃቸዋለሁ “ምን ያህል ሞከራችሁ?” “ምን ያህል ልባችሁን ሰጣችሁት?” ልባችን እንደ ጡንቻ ነው። በኃይል ልንለጥጠው እንችላለን። መንግስተ ሰማያትን በኃይል ተናጠቋት (ማቴዎስ 11፡12)። ጨካኞች ልትሆኑ ያስፈልጋችኋል። የክርስቶስን ተስፋ በዓይኖቻችሁ ፊት አጥብቃችሁ ያዙ። ያዙት! እንዳትለቁት! እስከመቼ? አስፈላጊ ሆኖ እስከተገኘ ጊዜ ድረስ። ተፋለሙት! ስለክርስቶስ ስትሉ እስክታሸንፉት ድረስ ተፋለሙት! ልጃችሁ ላይ የሆነ ነገር ሊወድቅበት እና ሊጫነው ቢል በእርግጠኝነት በሙሉ አቅማችሁ ትይዙታላችሁ እርዳታም ትጠይቃላችሁ።
ተደሰቱ:- በሚበልጥ እርካታ ተደሰቱ። በክርስቶስ የመደሰት አቅማችሁን አሳድጉ። በብዙዎች ውስጥ ምኞት የሚነግሠው ለክርስቶስ ጥቂት ፍላጎት ስላላቸው ብቻ ነው። በክርስቶስ ያለን ደስታ ጥቂት ስለሆነ በቀላሉ ወደ መታለል እንገባለን። “ይሄ እኔ አይደለሁም” ብቻ አትበሉ። ለኢየሱስ ያላችሁን ፍቅር ለማነሳሳት ምን እርምጃ ወስዳችኋል? ለደስታችሁ ተፋልማችኋል? ለውጥ ሊመጣ አይችልም ብላችሁ ተስፋ አትቁረጡ። የተፈጠራችሁት ወሲብን አጥብቃቸችሁ ከያዛችሁት በላይ በሙሉ ልባችሁ ክርስቶስን እንድትወድዱት ነው። ለኢየሱስ ያላችሁ ፍላጎት ጥቂት ከሆነ ደስታዎችን ማወዳደር በላያችሁ ላይ ያይላል። ስለሌላችሁ እርካታ እግዚአብሔርን ለምኑት። “በማለዳ ምሕረትህን እንጠግባለን በዘመናችን ሁሉ ደስ ይለናል ሐሤትም እናደርጋለን” (መዝሙር 90፡14)። ከዚያም በዓለም ሁሉ ላይ እጅግ ድንቅ የሆነውን ጌታ ማንነት እስክታዩ ድረስ ፈልጉት።
ዘወር ማለት:- ከሚያጋልጧችሁ ባህርያት እና ምንም ካለማድረግ ዘወር ብላችሁ ወደሚጠቅም ሥራ ግቡ። ምኞት በመዝናኖት ጓሮ ውስጥ የበለጠ ቶሎ ያድጋል። ልትሰሩት የምትችሉትን መልካምን ሥራ ፈልጉና በሙሉ ኃይላችሁ አድርጉት። “ለሥራ ከመትጋት አትለግሙ፤ በመንፈስ የምትቃጠሉ ሁኑ፤ ለጌታ ተገዙ” (ሮሜ 12፡11) “የምትደላደሉ፥ የማትነቃነቁም፥ የጌታም ሥራ ሁልጊዜ የሚበዛላችሁ ሁኑ” (1 ቆሮንቶስ 15፡58)። በሥራ ተጠመዱ። ተነሱና ሌላ ነገርን ሥሩ። ክፍላችሁን ጥረጉ። የለቀቀ ምስማር ካለ አጥብቁ። ደብዳቤ ጻፉ። እናም ሁሉንም ስለ ኢየሱስ ስትሉ አድርጓቸው። የተፈጠራችሁት ለመፍጠር እና ለመቆጣጠር ነው። ክርስቶስ የሞተላችሁ “መልካሙንም ለማድረግ የምትቀኑ” (ቲቶ 2፡14) እንድትሆኑ ነው። የሚያታልልን ምኞት ለመልካም ሥራ ባለ ቅንዓት ቀይሩት።
Originally Posted at DesiringGod.org, Translated by Joshua Terefe