በቁጥር 35 ላይ ሦስት ነገሮችን አስተውሉ።
1. ክርስቶስ አሁን እየወደደን ነው
ሚስት ስለሞተ ባሏ ከእርሱ ፍቅር ማንም አይለየኝም ልትል ትችላለች ። የፍቅሩ ትውስታ በሕይወቷ ሁሉ ጣፋጭ እና ኃይለኛ እንደሆነ ለመግለጽ ሊሆን ይችላል ። ጳውሎስ ግን እዚህ ጋር እያለ ያለው ይህን አይደለም ። በሮሜ 8፡34 ላይ በግልጽ ሲናገር “የሞተው፥ ይልቁንም ከሙታን የተነሣው፥ በእግዚአብሔር ቀኝ ያለው፥ ደግሞ ስለ እኛ የሚማልደው ክርስቶስ ኢየሱስ ነው” ይላል ። ጳውሎስ ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል ማለት የሚችለው ክርስቶስ በሕይወት ስላለ እና አሁንም ስለሚወድደን ነው ። በእግዚአብሔር ቀኝ ስላለ ስለእኛ እየገዛ ነው ። ደግሞም እየማለደልን ነው ። ማለትም የመዋጀቱ ያለቀ ሥራ እንደሚያድነን እና ወደ ዘላለም ደስታ እንደሚያመጣን እርግጥ እያደረገ ነው ። ፍቅሩ ትውስታ አይደለም ። ወደ ዘላለማዊ ደስታ እንዲያመጣን ሁሉን በሚችለው በሕያው የእግዚአብሔር ልጅ ከጊዜ ወደ ጊዜ የሚደረግ ድርጊት ነው።
2. የክርስቶስ ፍቅር ከመለየት ሊጠብቀን ስለሚቻለው ይህ ፍቅር ለአለም ሁሉ የሆነ ፍቅር አይደለም ነገር ግን በሮሜ 8:28 መሠረት እግዚአብሔርን ለሚወድዱት እንደ ሀሳቡም ለተጠሩት ለህዝቦቹ የተለየ ፍቅር ነው ።
ይሄ በኤፌሶን 5፡25 ላይ ያለው ፍቅር ነው:- “ባሎች ሆይ፥ ክርስቶስ ደግሞ ቤተ ክርስቲያንን እንደ ወደዳት ሚስቶቻችሁን ውደዱ” ይሄ ክርስቶስ ሙሽራው ለሆነችው ለቤተክርስትያን ያለው ፍቅር ነው ። ክርስቶስ ለሁሉም ፍቅር አለው ደግሞም የሚያድን እና የሚጠብቅ ፍቅር ደግሞ ለሙሽራው አለው ። በክርስቶስ ካመናችሁ የዚህ ሙሽራ አካል እንደሆናችሁ ታውቃላችሁ ። በክርስቶስ የሚያምን ማንኛውም ሰው ሁሉ ያለ ምንም መለያያት እኔ የሙሽራው ፣ የቤተክርስትያኑ እናም ቁጥር 35 ምንም ቢሆን ለዘላለም የተጠበቁት የተጠሩት እና የተመረጡት የሚላቸው ውስጥ አንድ አካል ነኝ ማለት ይችላል ።
3. ይሄ ሁሉን ቻይ እና የሚጠብቅ ፍቅር በሕይወት የሚደርሱ አደጋዎች እንዳይደርሱብን አያደርግም ። ነገር ግን በእግዚአብሔር ዘንድ ወዳለ ዘላለማዊ ደስታ ሊያደርሰን ይችላል ።
ሞት ሊደርስብን ይችላል ግን አይለየንም። ስለዚህ ጳውሎስ በ ቁጥር 35 ላይ “ሰይፍ” ከክርስቶስ ፍቅር ሊለየን አይችልም ሲል ብንሞት እንኳን ከክርስቶስ ፍቅር ልንለይ አንችልም ማለቱ ነው ።
ስለዚህ በቁጥር 35 ላይ ያለው ሀሳብ ሲጠቃለል:- ክርስቶስ ኢየሱስ ህዝቡን በሚያስደንቅ ሁሉን ቻይ እና በሁሉም ጊዜ በሚገለጥ ነገር ግን ከአደጋ ሁሉ ነፃ በማያደርግ ይሁን እንጂ በመገኘቱ ሆኖ በሚገጥሙን መከራዎች እና ሞት ውስጥ ለዘላለም ደስታ በሚጠብቅ ፍቅሩ እየወደደን ነው።
Originally Posted at DesiringGod.org, Translated by Joshua Terefe