“ያስረዳል” የሚለው የአሁን ጊዜ ገላጭ ሲሆን “ሞቶአልና” የሚለው ደግሞ ኃላፊ ጊዜ ገላጭ ነው። “ነገር ግን ገና ኃጢአተኞች ሳለን ክርስቶስ ስለ እኛ ሞቶአልና እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን የራሱን ፍቅር ያስረዳል”። የአሁን ጊዜ ገላጩ “ማስረዳት” አሁንም ሆነ ነገ መደረግ የሚቀጥል ድርጊት እንደሆነ ያመለክታል።
ኃላፊ ጊዜ ገላጩ ደግሞ “ሞቶአልና” የሚለው ክርስቶስ ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ እንደሞተ እና እንደማይደገም ያስረዳል። “ክርስቶስ ደግሞ ወደ እግዚአብሔር እንዲያቀርበን እርሱ ጻድቅ ሆኖ ስለ ዓመፀኞች አንድ ጊዜ በኃጢአት ምክንያት ሞቶአልና” (1 ጴጥሮስ 3፡18)።
ጳውሎስ ለምንድን ነው “ያስረዳል” ሲል የአሁን ጊዜ ገላጭን የተጠቀመው? ጳውሎስ “ነገር ግን ገና ኃጢአተኞች ሳለን ክርስቶስ ስለ እኛ ሞቶአልና እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን የራሱን ፍቅር አስረድቷል" (ኃላፊ ጊዜ ገላጭ) ይላል ብዬ ነበር የምጠብቀው ። የክርስቶስ ሞት የእግዚአብሔር ፍቅር ማስረጃ አልነበረምን? ይህስ ማስረጃ ባለፈ ጊዜ የሆነ ነገር አይደለም? ታዲያ ለምንድን ነው ጳውሎስ “አስረድቷል” በማለት ፈንታ “ያስረዳል” የሚለው?
እንደሚመስለኝ ከሆነ ከዚህ ክፍል የተወሰኑ ቁጥሮች ቀደም ብሎ ፍንጭ የሚሆን ነገር ተቀምጧል። “ይህም ብቻ አይደለም፥ ነገር ግን መከራ ትዕግሥትን እንዲያደርግ፥ ትዕግሥትም ፈተናን ፈተናም ተስፋን እንዲያደርግ እያወቅን፥ በመከራችን ደግሞ እንመካለን፤ በተሰጠንም በመንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ፍቅር በልባችን ስለ ፈሰሰ ተስፋ አያሳፍርም" (ሮሜ 5፡3-5)። በሌላ ቃል እግዚአብሔር በሚያሳልፈን ነገር ውስጥ ሁሉ ግቡ ተስፋ ነው። በመከራዎች ውስጥ የማይነቃነቅ ተስፋ እንዲሰማን ይፈልጋል።
ነገር ግን እንዴት እንችላለን? መከራዎች በእራሳቸው ተስፋ አስቆራጭ ናቸው። በእራሳቸው ተስፋ እንዲሰማን የሚያደርጉ ከሆነ መከራ ሊሆነ አይችሉም። ነገር ግን በመከራ ውስጥ በምናልፍበት ጊዜ በተስፋ የመበርታት ምስጢሩ ምንድን ነው?
ጳውሎስ በሚቀጥለው መስመር ላይ ሲናገር “በተሰጠንም በመንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ፍቅር በልባችን ስለ ፈሰሰ ተስፋ አያሳፍርም” ይላል። የእግዚአብሔር ፍቅር “በልባችን ውስጥ ፈስሷል”። የዚህ ግስ ጊዜ አመልካች የሚገልጸው የእግዚአብሔር ፍቅር በልባችን ውስጥ ባለፈ ጊዜ (በዳንን ጊዜ) እንደፈሰሰ እና አሁንም እንዳለ እና እንደሚሰራ ነው።
ስለዚህ የጳውሎስ ዋና ነጥብ ከመንፈስ ቅዱስ የሆነ የደኅንነት እርግጠኝነት እና በእግዚአብሔር ፍቅር መደሰት በመከራ ውስጥ በተስፋ የምናድግበት ምስጢር እንደሆነ ነው። መከራ ትዕግሥትን ፣ መጽናትን ፣ ፈተናን እና የማያሳፍርን ተስፋ የሚያደርገው በመንገዳችን እያንዳንዷ ነጥብ ላይ የእግዚአብሔር መንፈስ በመከራችን ውስጥ ስለእግዚአብሔር ፍቅር ማረጋገጫ ስለሚሰጠን ነው።
አሁን ጳውሎስ በቁጥር 8 ላይ”. . . እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን የራሱን ፍቅር ያስረዳል” በማለት ለምን የአሁን የጊዜ ገላጭ እንደተጠቀመ ማየት እንችላለን። ይሄ በቁጥር 5 ላይ የተገለጠው የመንፈስ ቅዱስ ሥራ ነው። እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በልባችን ላይ የእግዚአብሔርን ፍቅር እያፈሰሰ እና እየዘረጋ ነው።
እግዚአብሔር ባለፈ ጊዜ ስለኃጢያታችን ልጁን ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ እንዲሞት በመስጠት ፍቅሩን ገልጾልናል (ቁጥር 8)። ይሁን እንጂ ትዕግስት ፈተና እና ተስፋ እንዲኖሩን ቢያስፈልግ ይሄን ያለፈ ፍቅር የአሁን ጊዜ እውነታ (ዛሬ እና ነገ) አድርገን እንድንቀበለው እንደሚያስፈልግ ያውቃል። ስለዚህ በቀራንዮ ላይ ብቻ ሳሆን አሁንም በመንፈሱ ማስረዳቱን ቀጥሏል። ይህንንም ያደረገው የልቦናችንን ዓይኖች የመስቀሉን ክብር “እንዲያዩና እንዲቀምሱ” በመክፈት እንዲሁም በክርስቶስ ኢየሱስ ካለ ከእግዚአብሔር ፍቅር ምንም ሊለየን እንደማይችል (ሮሜ 8፡39) ማስረገጫ በመስጠት ነው።
ከእናንተ ጋር አብሬ የፍቅሩን ማስረዳት ሙሉ ደስታ የምሻ ጆን ፓይፐር።
Originally Posted at DesiringGod.org, Translated by Joshua Terefe