ሙዚቃዊ ደስታ እና ለሁሉም ነገር ማመስገን ብቻ ሳይሆን ለእያንዳንዱ ፍላጎት ደግሞ በፍቅር መገዛትን ይጨምራል (ቁጥር 21)። ደስታ፣ ምስጋና እና ትሁት ፍቅር በመንፈስ ቅዱስ መሞላት ምልክቶች ናቸው። እዚህ ላይ ከመጽሐፍ ላይ (ሐዋርያት ሥራ 2፡4 ፤ 4፡8 ፡ 13፡9 ይመልከቱ) የመመስከር ድፍረትን መጨመር እንችላለን። መንፈስ ቅዱስ የሚፈስን ደስታ ፣ የማያቋርጥን ምስጋና እና ትሁት ፍቅርን በውስጡ እያፈራ ማንም ደፋር እና የሚጓጓ ከመሆን ሊጎድል አይችልም። በመንፈስ ቅዱስ መሞላት አቤት እንዴት ያስፈልገናል! እንፈልገው! ፈጽመን እንሻው!
እንዴት?
በቅርብ ካለው ንጽጽር እስቲ እንጀምር:- መንፈስ ይሙላባችሁ እንጂ በወይን ጠጅ አትስከሩ! በወይን የምትሰክሩት እንዴት ነው? ብዙ መጠን ያለው ወይን በመጠጣት። በጳውሎስ ዘመን የነበረው ወይን እጅግ ደካማ ስለነበር መስከር ካስፈለጋችሁ ለረጅም ሰዓታት መጠጣት ይኖርባችኋል። ታዲያ እኛስ በመንፈስ ቅዱስ እንዴት መስከር (መሞላት) እንችላለን? መልሱ አሁንም በመጠጣት! በብዛት በመጠጣት። ጳውሎስ በ1 ቆሮንቶስ 12፡13 ሲናገር “እኛ ሁላችንም . . . አንዱን መንፈስ ጠጥተናል” ይላል። ኢየሱስም “ማንም የተጠማ ቢኖር ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ፤ በእኔ የሚያምን መጽሐፍ እንዳለ፥ የሕይወት ውኃ ወንዝ ከሆዱ ይፈልቃል ብሎ ጮኸ። ይህን ግን በእርሱ የሚያምኑ ሊቀበሉት ስላላቸው ስለ መንፈስ ተናገረ” (ዮሐንስ 7፡37-39)
መንፈስ ቅዱስን እንዴት መጠጣት እንችላለን? ጳውሎስ ሲናገር “እንደ መንፈስ ፈቃድ የሚኖሩ የመንፈስን ነገር ያስባሉ” (ሮሜ 8፡5) ብሏል። መንፈስ ቅዱስን ልንጠጣ የምንችለው የመንፈስን ነገር በማሰብ ነው። “ማሰብ” ሲል እንዴት አይነት ነው? ቆላስይስ 3፡1-2 ሲናገር “. . . በላይ ያለውን እሹ። በላይ ያለውን አስቡ እንጂ በምድር ያለውን አይደለም” ይለናል። “ማሰብ” ሲል መሻት ፣ ትኩረታችሁን ወደ አንድ ነገር ማዞር ፣ ልብን ማሳረፍ (ፊሊጲስዩስ3፡19) ፣ ስለሆነ ነገር መትጋት እና በአንድ ነገር መያዝ ማለት ነው። ስለዚህ መንፈስ ቅዱስን መጠጣት ማለት የመንፈስን ነገር ማሰብ ፣ ትኩረትን ወደ መንፈስ ነገር ማዞር እና ስለ መንፈስ ነገር ትጉህ መሆን ማለት ነው።
“የመንፈስ ነገር” ምንድን ናቸው? ጳውሎስ በ 1 ቆሮንቶስ 2፡14 ላይ “ለፍጥረታዊ ሰው የእግዚአብሔር መንፈስ ነገር ሞኝነት ነውና አይቀበለውም” ሲል ስለ በመንፈስ ቅዱስ ስለተመሩት (2፡13) የእራሱ ትምህርቶች እና ስለ እግዚአብሔር ሃሳብ እና መንገድ እንዲሁም እቅዱ (2፡8-10) እየተናገረ ነው። ስለዚህ “የመንፈስ ነገር” የምንላቸው ሐዋርያት ስለ እግዚአብሔር ያስተማሩት ትምህርት ነው። ኢየሱስም ደግሞ “እኔ የነገርኋችሁ ቃል መንፈስ ነው ሕይወትም ነው” ብሎ እንደተናገረ የኢየሱስም ትምህርቶች “የመንፈስ ነገር” የምንላቸው ነው።
ስለዚህ መንፈስ ቅዱስን መጠጣት ማለት ስለመንፈስ ነገር ማሰብ ማለት ነው። ስለ መንፈስ ነገር ማሰብ ማለት ደግሞ ሐዋርያት ስለ እግዚአብሔር ወዳስተማሩት እና ወደ ኢየሱስ ትምህርቶች ማተኮር ነው። ይህንን ለረጅም ጊዜ ማድረግ ብንችል በመንፈስ እንሰክራለን። የበለጠ ከመንፈስ ቅዱስ ሱስ ይይዘናል። ኬሚካል ላይ ከመደገፍ ይልቅ መንፈስ ላይ በሚደንቅ ሁኔታ መደገፍን እንጀምራለን።
አንድ ተጨማሪ ጉርሻ:- መንፈስ ቅዱስ ፍቃድ ያለው አካል/ማንነት ስለሆነ እንደፈለገ መምጣት እና ወደፈለገበት መሄድ በመቻሉ (ዮሐንስ 3፡8) እንደ ወይን አይደለም። ስለዚህ ሉቃስ 11፡13 መጨመር አለበት። ኢየሱስም ለደቀ መዛሙርቱ “እንኪያስ እናንተ ክፉዎች ስትሆኑ ለልጆቻችሁ መልካም ስጦታ መስጠት ካወቃችሁ፥ በሰማይ ያለው አባት ለሚለምኑት እንዴት አብልጦ መንፈስ ቅዱስን ይሰጣቸው?” ይላቸዋል (ሉቃስ 11፡13)። ስለዚህ መንፈስ ቅዱስን እንድንሞላ ካስፈለገን እንዲሰጠን መጸለይ አለብን። ጳውሎስም በኤፌሶን 3፡19 ላይ ለኤፌሶን ሰዎች ያደረገው ይህንኑ ነበር። አማኞች “እስከ እግዚአብሔር ፍጹም ሙላት ደርሰው እንዲሞሉ” በሰማይ ያለውን አባቱን ይጠይቃል። እየጠጣችሁ ጸልዩ። እየጠጣችሁ ጸልዩ። እየጠጣችሁ ጸልዩ።
Originally Posted at DesiringGod.org, Translated by Joshua Terefe