1. ሉአላዊ ድንጋጌ
እግዚአብሔር ምንም እንኳን እኛ ሃሳቡ ባይኖረንም እርሱ ግን እንድንደርስበት የሚፈልጋቸው ቦታዎች ላይ እንድንደርስ በሉአላዊ ትዕዛዙ ሁኔታዎችን ያመቻቻል። ለምሳሌ ጳውሎስ እና ሲላስ እራሳቸውን ወህኒ ቤት አገኙት ፤መጨረሻውም የጠባቂው እና ቤተሰቡ ድነት ነበር (ሐዋሪያት ሥራ 16፡24-34)። ይሄ የጳውሎስ አላማ ባይሆንም የእግዚአብሔር ግን ነበር። እግዚአብሔር እኛ ያላሰብናቸው ወይንም ያላቀድናቸው ቦታዎች ላይ ያስቀምጠናል ፤ ይህንን ብዙ ጊዜ ያደርጋል ። ይሄ በሉአላዊ ድንጋጌ ሲመራን ነው። ሁሉንም በማጠቃለሉ ምክንያት (የእግዚአብሔር ድንጋጌ ሁሉንም ውሳኔዎቻችንን ስለሚያጠቃልል) እና ያለመከልከል ስለሚፈጸም (የእግዚአብሔር ምንም ሃሳብ ሊከለከል ስለማይችል ኢዮብ 42፡2 ) ከሌሎቹ ሦስቱ ምሪቶች ይለያል። ሌሎቹ ሦስቱ ምሪቶቹ የእኛን በንቃት መከተል ይጠይቃሉ።
2. አቅጣጫ
ይሄኛው ደግሞ እግዚአብሔር የመጽሐፍ ቅዱስን ትዕዛዞች እና ትምህርቶች በመስጠት የሚመራን ነው። ማድረግ ያለብንን እና ማድረግ የሌለብንን እንድናውቅ ይመሩናል። ለዚህም አስርቱ ተዕዛዛት ምሳሌ ናቸው። አትስረቅ። አትግደል። አትዋሽ። ወይንም የተራራው ስብከት ጠላቶቻችሁን ውደዱ። ወይንም ደግሞ በመልዕክቶች ውስጥ:- በመንፈስ ቅዱስ ተሞሉ። ትህትና ልበሱ። ይሄ የአቅጣጫ ምሪት ነው። እግዚአብሔር መንገዱን በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ገልጾአል።
3. መለየት
ብዙዎቹ የምንወስናቸው ውሳኔዎች በግልጽ መጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተጻፉ አይደሉም። መለየት ስንል ለተለያዩ ጉዳዮቻችን የመጽሐፍ ቅዱስን እውነቶች በመንፈሳዊ ቅርበት በማጤን የእግዚአብሔርን ምሪት የምንከተልበት ነው። ሮሜ 12፡2 ይህንኑ ይገልጻል “የእግዚአብሔር ፈቃድ እርሱም በጎና ደስ የሚያሰኝ ፍጹምም የሆነው ነገር ምን እንደ ሆነ ፈትናችሁ ታውቁ ዘንድ በልባችሁ መታደስ ተለወጡ እንጂ ይህን ዓለም አትምሰሉ”። በዚህን ጊዜ እግዚአብሔር ምን ማድረግ እንዳለባችሁ አይደነግግም። ነገር ግን መንፈሱ እግዚአብሔርን የበለጠ ሊያከብር ወደሚችለው እና ለሌሎች ጥቅም ወደሚሆነው ልባችን እንዲያዘነብል አዕምሮአችንን እና ልባችንን በቃሉ ውስጥ እና በፀሎት ይቀይረዋል።
4. ትዕዛዝ
ይሄ ያልተለመደው የእግዚአብሔር ምሪት መንገድ ነው። ማድረግ ስላለብን ነገር በቀላሉ ትዕዛዝ ይሰጠናል። ለምሳሌ በሐዋሪያት ሥራ 8፡26 ላይ “የጌታም መልአክ ፊልጶስን ተነሥተህ በደቡብ በኩል ከኢየሩሳሌም ወደ ጋዛ ወደሚያወርደው ምድረ በዳ ወደ ሆነ መንገድ ሂድ አለው።” በሐዋሪያት ሥራ 8፡29 ላይ ደግሞ “መንፈስም ፊልጶስን ወደዚህ ሰረገላ ቅረብና ተገናኝ አለው።"
* * *
ሦስት ነገሮችን አስተውሉ። በመጀመሪያ በእግዚአብሔር ሉአላዊ ድንጋጌዎች ላይ ሁል ጊዜ ማረፍ አለብን። የምንወደው ከሆነ እና እንደስሙ ተጠርተን ከሆነ ነገር ሁሉ ለበጎ ነው የሚደረግልን (ሮሜ 8፡28)።ይሄ ከሕይወታችን ውስጥ ፍርኃትን አስወግዶልን በ “አቅጣጫ” ውስጥ በ“መለየት” ውስጥ እና በ”ትዕዛዙ” ውስጥ ከሚገኘው ምሪቱ ጋር ሰላም አንሆናለን።
በመቀጠል እግዚአብሔር በ“አቅጣጫ”፣ በ“መለየት” እና በ”ትዕዛዝ” ከሚመራን መንገድ ተቃራኒ በሆነ መልኩ በሉአላዊ ድንጋጌው ሊመራ የሚችልበት ምልከታ አለ። በሌላ አገለለጽ “አትግደሉ” ብሎ አቅጣጫን ይሰጠናል ነገር ግን የልጁን ሞት ሲደነግግ ደግሞ እንመለከታለን (ሐዋሪያት ሥራ 4፡28)። እዚህ ጋር ረቂቅ ነገሮች አሉ፤ ነገር ግን በብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ላይ እግዚአብሔር በቃሉ ውስጥ የከለከላቸውን ነገሮች እንዲከሰቱ ሲፈቅድ ተገልጾአል።
በመጨረሻም ከላይ በተጠቀሱት ዝርዝሮች ውስጥ ከታች ወደላይ በምንመለከትበት ጊዜ ከእግዚአብሔር ጋር በትክክል እየሄድን እንዳለን ድፍረትን እናገኛለን። በግላችን የምንረዳው “የትዕዛዝ” ምሪት ከሌሎቹ የምሪት አይነቶች የተለየ ብዙውን ጊዜ የማይገጥም ደግሞም በቀላሉ ስህተት በሆነ መልኩ ሊወሰድ የሚችል ነው። በእዚህ መልኩ የእግዚአብሔርን ፈቃድ አውቀናል ብለን ለመናገር የሚኖረን እርግጠኝነት ከሌሎቹ ከእግዚአብሔር ቃል ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ካላቸው ሦስቱ የምሪት አይነቶች ጋር ሲስተያይ አነስተኛ ነው። የመጽሐፍ ቅዱስ መርሖችን ምሪት ተጠቅመን “በመለየት” የምንወስደው ቁርጥ ውሳኔ በግልጽ የተቀመጡትን የመጽሐፍ ቅዱስ “አቅጣጫዎች” ጋር ሲስተያይ ደግሞ ያነሰ ድፍረትን ይሰጣል። እግዚአብሔር ሉአላዊ እንደሆነ እና ነገሮችን ሁሉ እንደሚመራ የምናውቀው እውነት ደግሞ ከሁሉም ስር መሰረት የሆነ ዓለታችን ነው። ልናርፍበት የተገባ መልካም ስፍራ ነው።
Originally Posted at DesiringGod.org, Translated by Joshua Terefe