ጠላታችን በመከራ ውስጥ ስናልፍ ሊከሰን ይፈልጋል። አንድ ጥፋት ስላጠፋን ወደ እግዚአብሔር መቅረብ እንደማንችል እንዲሰማን ይፈልጋል። ነገር ግን በኢየሱስ ምክንያት አሁን ከእግዚአብሔር ጋር ሰላም አለን። በእርሱም ያለን እምነት በጸጋው እንድንቆም ያደርገናል። ከላይ ያለው ክፍል እንደጸደቅን ይናገራል (ይህም ማለት ኢየሱስ የከፈለልን ዋጋ ኃጢያት አድርገን የማናውቅ እስኪመስል ድረስ ከዕዳ ነፃ አድርጎናል።) መጽደቃችን የዕዳችን ዋጋ መከፈሉ ብቻ አይደለም ነገር ግን ወደ ጸጋው ዙፋን እንድንቀርብ ፍቃድ ማግኘታችን ጭምር ነው። እንዴት ያለ ድንቅ ስጦታ ነው የተቀበልነው!
በመንገዳችን ከሚመጡት ውጊያዎች ለመጠበቅ እና ልባችንን ለማጠንከር ያስችለን ዘንድ በዚያን ጊዜ በውስጣችን የፈሰሰውን ፍቅሩን ደግሞ እንድንቀበል ያስፈልጋል። በፍቅር የተሞላ ልብ የሚደርስበትን ማንኛውም ጥቃት መዋጋት ይችላል። በዚህን ወቅት መንፈስ ቅዱስ ከምን ጊዜውም በላይ እንዲሞላን ፣ በውስጣችን እንዲኖር እና ኃይሉን እንዲያሳየን ያስፈልገናል። ይህ ኃይል ጠላት ወደ እኛ የሚወረውረውን ማንኛውንም ኃፍረት ያሸንፋል። መልካምንም ሥራ እንድናፈራ መጽናትን ይሰጠናል። በዚህ ሁሉ ውስጥ ተስፋ ውጤቱ ነው።
2. ፍርሃት
አይቀበለኝም የሚል ፍርሃት ይሁን የቅጣት ፍርሃት ወይንም ያለመሳካት ፍርሃት ቢሆን ፍርሃት ወደ እግዚአብሔር እንዳንሄድ ይከለክለናል። ወደ እግዚአብሔር መቅረብ ከፈለግን የሚሰማን ፍርሃትም ከጠላት እንደሆነ ልናስተውል ይገባል። 2 ጢሞቴዎስ 1፡7 “እግዚአብሔር የኃይልና የፍቅር ራስንም የመግዛት መንፈስ እንጂ የፍርሃት መንፈስ አልሰጠንምና” ይላል። ይህ ፍርሃት ከእግዚአብሔር አይደለም። ከእግዚአብሔር ስላልሆነ ደግሞ ስንጠብቃቸው የነበሩትን ቅጣት እና አለመሳካት እንዲሆኑብን አይስማማም። እርሱ ከእናንተ ጋር ነው። ይወድዳችኋል። ወደ ፍቅር ስንጠጋ ያ ሁሉ ፍርሃት እንደሚጠፋ እንረዳለን። 1 ዮሐንስ 4፡18-19 “ፍጹም ፍቅር ፍርሃትን አውጥቶ ይጥላል እንጂ በፍቅር ፍርሃት የለም፥ ፍርሃት ቅጣት አለውና፤ የሚፈራም ሰው ፍቅሩ ፍጹም አይደለም። እርሱ አስቀድሞ ወዶናልና እኛ እንወደዋለን” ይላል። በቀረብነው ቁጥር የበለጠ እየወደድነው እንመጣለን።
3. ቸልተኝነት
አንዳንዶቻችን እግዚአብሔር ማን እንደሆነ አናውቅም። ስለባህሪያቶቹ ቸልተኞች ነን። ማን እንደሆነ ካላወቅን ደግሞ እንዴት መቅረብ እንዳለብን አናውቅም። ከእግዚአብሔር አንደኛው ድንቅ ባህሪ ውስጥ በሁሉም ቦታ ሁል ጊዜ መገኘት መቻሉ ነው። ከመገኘቱ ልንሰወር የምንችልበት ስፍራ የለንም። መዝሙረኛው በመዝሙር 139፡7-12 “ከመንፈስህ ወዴት እሄዳለሁ? ከፊትህስ ወዴት እሸሻለሁ? ወደ ሰማይ ብወጣ፥ አንተ በዚያ አለህ። ወደ ሲኦልም ብወርድ፥ በዚያ አለህ። እንደ ንስር የንጋትን ክንፍ ብወስድ፥ እስከ ባሕር መጨረሻም ብበርር፥ በዚያ እጅህ ትመራኛለች፥ ቀኝህም ትይዘኛለች። በውኑ ጨለማ ትሸፍነኛለች ብል፥ ሌሊት በዙሪያዬ ብርሃን ትሆናለች ጨለማ በአንተ ዘንድ አይጨልምምና፥ ሌሊትም እንደ ቀን ታበራለችና እንደ ጨለማዋ እንዲሁ ብርሃንዋ ነው” ብሎ እንደዘመረው ነው።
እግዚአብሔር በማንኛውም ቦታ ሁል ጊዜ የሚገኝ ከሆነ ወደ ጸጋው ዙፋን ለመቅረብ የሚያስፈልገን መጸለይ ብቻ ነው። በጉዟችን አጋር እና ጓደኛ ሊሆነን እየጠበቀን ነው። እግዚአብሔርን በቃሉ ውስጥ ልናውቀው ያስፈልገናል። ቃሉን ማንበብ በዓለም ላይ ያለን ታላቅ መዝገብ እንደማግኘት ነው። ማን እንደሆነ ባወቅን ቁጥር በመገኘቱ ፊት ለመሆን የበለጠ እንፈልጋለን። የዚያን ጊዜ የዕብራውያን ጸሃፊ እንዳለው ወደ እግዚአብሄር በድፍረት መቅረብ እንጀምራለን። በዚህ ዓመት እርሱን የበለጠ ማወቅን አላማችን እናድርግ!
ወደ እግዚአብሔር መቅረብ (ክፍል 1)
Translated by Joshua Terefe